ሂሳዊ የማንበብ ብልሃቶች የተማሪዎችን አንብቦ የመረዳት ችሎታንና የማንበብ ተነሳሽነት ለማሻሻል ያላቸው አስተዋጽኦ፤ በዘጠነኛ ክፍል ተተኳሪነት
Abstract
የዚህ ጥናት ዋና ዓላማ ሂሳዊ የማንበብ ብልሃቶች የተማሪዎችን አንብቦ የመረዳት ችሎታ እና የማንበብ ተነሳሽነት በማጎልበት ረገድ ያላቸውን አስተዋጽኦ በከፊል ፍትነታዊ ምርምር መፈተሽ ነው፡፡ ከሂሳዊ የማንበብ ብልሃቶች መካከል ቅድመ ቅኝት፣ አውዳዊ ማድረግ፣ ለመረዳትና ለማስታወስ መጠየቅ፣ እሴቶቻችንን በሚፈታተኑ ጉዳዮች ላይ ፅብረቃ ማድረግ፣ ዋና ሐሳብን ማውጣትና ማጠቃለል፣ የፀሐፊውን የመከራከሪያ ሐሳቦች መመዘን እንዲሁም ተዛማጅ ጽሑፎችን ማወዳደርና ማነፃፀር ትኩረት የተደረገባቸው ናቸው፡፡ ዓላማውን ለማሳካት ጎንደር ከተማ የሚገኘው የፋሲለደስ አጠቃላይ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት በአመቺ ንሞና ዘዴ ተመርጧል፡፡ በትምህርት ቤቱ ከሚገኙ ሃያ ሁለት የዘጠነኛ ክፍል ምድቦች መካከል ሁለት ምድብ ተማሪዎች በቀላል የዕጣ ንሞና ተለይተዋል፡፡ ከእነሱም በቅድመ እና ድኅረ ትምህርት አንብቦ የመረዳት ፈተና እና የማንበብ ተነሳሽነት በሚለካ የጽሑፍ መጠይቅ አማካይነት የጥናቱ መረጃዎች ተሰብስበዋል፡፡ የተሰበሰቡት መረጃዎችም ከተደራጁ በኋላ በባዕድ ናሙና ቲ-ቴስት ተተንትነዋል፡፡ በውጤት ትንተናው መሰረትም የሙከራው ቡድን የድኅረ ትምህርት አንብቦ የመረዳት ፈተና ውጤት ከቁጥጥር ቡድኑ አንብቦ የመረዳት ፈተና ውጤት በልጦ ጉልህ ልዩነት (ቲ (111) = 4.313 P = 0.000) አሳይቷል፡፡ በተመሳሳይ መልኩ የሙከራው ቡድን የድኅረ ትምህርቱ የማንበብ ተነሳሽነት አማካይ ውጤት ከቁጥጥሩ ቡድን የድኅረ ትምህርት የማንበብ ተነሳሽነት አማካይ ውጤት በልጦ ጉልህ ልዩነት (ቲ (111) = 3.614፤ P = 0.000) እንዳለ አመላክቷል፡፡ ከዚህም በመነሳት ሂሳዊ የማንበብ ብልሃቶች የተማሪዎችን አንብቦ የመረዳት ችሎታ እና የማንበብ ተነሳሽነት ለማጎልበት አስተዋጽኦ አላቸው ወደሚል መደምደሚያ ላይ ተደርሷል፡፡ በመጨረሻም ከድምዳሜው በመነሳት ለመምህራን እና ለተመራማሪዎች ልዩ ልዩ አስተያየቶች እንዲቀርቡ ተደርጓል፡፡
ቁልፍ ቃላት፤ ሂሳዊ ንባብ፣ ሂሳዊ የማንበብ ብልሃቶች፣ አንብቦ መረዳት፣ የማንበብ ተነሳሽነት
Downloads

This work is licensed under a Creative Commons Attribution-NonCommercial-NoDerivatives 4.0 International License.