የስርዓተ-ፆታ ሚናዎች አገነባብ ትንተና በዶርዜ ማህበረሰብ የጋብቻ ከበራ ልማድ
Abstract
ይህ ጥናት “የሥርዓተ-ፆታ ሚናዎች አገነባብ ትንተና በዶርዜ ማኅበረሰብ የጋብቻ ከበራ ልማድ” በሚል ርዕስ የቀረበ ነው፡፡ የጥናቱ ዐቢይ ዓላማ የዶርዜ ማኅበረሰብን የጋብቻ ከበራ ልማድ ከሥርዓተ-ፆታ ሚናዎች አገነባብ አንጻር መመርመር ሲሆን፤ በጋብቻ ሥነ-ስርዓቱ ውስጥ የሴቶችን እና የወንዶችን ተግባራት መለየት፤ እና በጋብቻ ሂደቱ ውስጥ የሚከወኑ ልማዶች እና ትዕምርቶች ለስርዓተ-ፆታ አገነባብ ያላቸውን አንድምታ ማብራራት የሚሉ ዝርዝር ዓላማዎችን አካቷል፡፡ እነዚህን ዝርዝር ዓላማዎች ከግብ ለማድረስ የመስክ መረጃዎች በቃለመጠይቅ፣ በተተኳሪ ቡድን ውይይት እና በምልከታ ዘዴዎች ተሰብስበዋል፡፡ ጥናቱ አይነታዊ የምርምር ሥነዘዴን በመከተል እና ኢትኖግራፊያዊ የምርምር ስልትን በመተግበር የመስክ መረጃዎች በይዘት ተደራጅተዋል፡፡ እነዚህ መረጃዎች በማኅበራዊ ሚና (Social Role Theory) እና በትዕምርታዊ መስተጋብር (Symbolic Interactionism) ንድፈ ሃሳቦችን መሰረት በማድረግ በገላጭ እና በትርጓሜ (Interpretive) ስልት ተተንትነዋል፡፡ በትንታኔው መሰረትም፤ የዶርዜ ማህበረሰብ በሚከውናቸው የጋብቻ ከበራዎች ውስጥ ፆታን መሰረት ባደረጉ ተግባራት እና ትዕምርቶች የታጀቡ ናቸው፡፡በዚህም መሰረት፤ በከበራዎቹ ውስጥ ወንዶች የስርዓት መሪ፣ ፈፃሚ እና አቅራቢ፤ ሴቶች ደግሞ አሰናጅ እና ደጋፊ ሆነው ቀርበዋል ፡፡ በእነዚህ ከበራዎች ውስጥ ጎልተው በታዩ ዘር የመተካት፣ ውሳኔ የመስጠት፣ የታዛዥነት እና አክባሪነት እንዲሁም የመንከባከብ ይዘቶች ውስጥ ወንድነት እና ሴትነት በተለያየ መልክ መታዬታቸውን ጥናቱ አረጋግጧል፡፡ በዚህም በአብዛኛው ወንዶች የመሪነት፣ የውሳኔ ሰጪነት እና የአቅራቢነት ሚናቸው ጎልቶ ሲታይ፣ ሴቶች ደግሞ የተንከባካቢነት እና የደጋፊነት ሚና እንዳላቸው በጥናቱ ለማረጋገጥ ተችሏል፡፡
ቁልፍ ቃላት፡- ስርዓተ-ፆታ፣ የስርዓተ-ፆታ ሚና፣ ጋብቻ፣ ከበራ እና ልማድ፣ ዶርዜ
Downloads
Copyright (c) 2026 Ethiopian Journal of Business and Social Sciences

This work is licensed under a Creative Commons Attribution-NonCommercial-NoDerivatives 4.0 International License.